• Sun. Feb 15th, 2026

የአብይ መንግሥት የፀጥታና የደህንነት አካላት በሰላማዊ ዜጎች ላይ የሚያደርሱትን ጭፍጨፋ ኦነግ – ኦነሠ በጥብቅ ያወግዛል (የኦነግ-ኦነሠ ጋዜጣዊ መግለጫ)

Jul 8, 2022

 የአብይ መንግሥት የፀጥታና የደህንነት አካላት በሰላማዊ ዜጎች ላይ የሚያደርሱትን ጭፍጨፋ ኦነግ ኦነሠ በጥብቅ ያወግዛል::

(የኦነግኦነሠ ጋዜጣዊ መግለጫ)

በቄለም ወለጋ ዞን በሃዋ ገላን አካባቢ በገዳዩ የብልጽግና ፓርቲ መንግስት በሰላማዊ ዜጎች ላይ ሌላ አሰቃቂ ጭፍጨፋ ተፈፅሟል። በኦሮሚያ ክልል በቄለም ወለጋ ዞን በሃዋ ገላን በሰላማዊ ሰዎች ላይ የተፈጸመውን ግድያ የኦሮሞ ነጻነት ግንባር — የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት በፅኑ የሚያወግዝ ሲሆን ለተጎጂ ወገኖቻችንም የተሰማንን ጥልቅ ሀዘን እንገልፃለን!

ይሄንን ጭፍጨፋ በተመለከተም በሚከተሉት ጉዳዮች ላይ ትኩረት ማድረግ እንፈልጋለን:-

1ኛ. አብይ አህመድ እና ‘ሚዲያዎቹ’ ከቶውንም መታመን የለባቸውም፣ በአገዛዙ ሚዲያዎች እና ዘገባዎቻቸው ላይ ተመስርተው ዘገባ ።የሚሰሩ የአለም አቀፍ የሚዲያ ተቋማትም ሊታመኑ አይገባም።

በርግጥ ጠ/ሚ አብይ አህመድ አሊ በግልና እሱም ከሚመራው የመገናኛ ብዙሀኖች ከሚፈሱት የማያባራና አሳፋሪ ውሸቶች ብዛት ምክንያት አብዛኛው ህዝባችን እና የአለም አቀፉ ማህበረሰብ አገዛዙን እና አመራሩን በቁም ነገር መመልከት ያቆሙ መሆናቸው ገሀድ እየሆነ የመጣ ቢሆንም በአገዛዙ የሚዲያ ዘገባዎች እና የአመራሩ መግለጫዎች ላይ በመመሥረት ዜናና ትንተናዎችን የሚያቀርቡ አንዳንድ የአለምአቀፍ ሚዲያዎችም እንዳሉ ታዝበናል። ይህ በአስቸኳይ መታረም አለበት።

ለምሳሌ ጭፍጨፋው ከመፈፀሙ ከአራት ቀናት በፊት እ.ኤ.አ. ሐምሌ 1 ቀን 2022 የአገዛዙ የኮሚኒኬሽን ምኒስቴር ምኒስትር ለአለም እንደተናገሩት የሀገር መከላከያው ፣የፌደራል ፖሊስ ፣የኦሮሚያ ልዩ ሃይል እና የአካባቢ ሚሊሻ በጥምረት የቄለም ወለጋ ፣የምዕራብ ወለጋ እና ሆሮ ጉዱሩ ወለጋ ዞኖች ውስጥ የሚገኙ ሁሉንም ወረዳዎች ሙሉ በሙሉ መቆጣጠራቸውንና አገዛዙ በምዕራብ ኦሮሚያ ያለውን ወታደራዊ አቋም በአስተማማኝ ደረጃ አጠናክሮ መቀጠሉን ለህዝቡ በአደባባይ መግለፃቸው ይታወሳል። በዚህ ተቃራኒ ግን አገዛዙ ሙሉ በሙሉ ተቆጣጥሬያለሁ ባለው በቄለም ወለጋ በሰላማዊ ዜጎች ላይ ጭፍጨፋ የፈጸመው የኦሮሞ ነፃነት ሠራዊት ነው የሚል የውሸት መግለጫ በፊንፊኔ ከሚገኙ ባለስልጣናት ተሰጥቷል:: በሚገርም መልኩ ሁለቱም እወጃዎቻቸው ውሸት ቢሆኑም እነዚህ ሚዲያዎች ግን ይህንን የተጣረዘ ዘገባ እንኳ ጥያቄ ውስጥ አላስገቡም:: አገዛዙ በርግጥ በምንም አካባቢ ላይ ሙሉ ቁጥጥር ያልነበረውና የሌለው ሲሆን ከቦታዎች ተደራሽነት አንፃር ሀይላችን ካልተቆጣጠራቸው አንዳንድ ቦታዎች መካከል ይህ ግፍ የተፈፀመበት አካባቢ አንዱ ነው:: በአጠቃላይ ከአብይ አህመድ እና ከሚዲያ ማሽኑ የሚመጣውን ማንኛውም ነገር የሚታመንበት ምንም ምክንያት የሌለ መሆኑን ሁሉም የሚመለከተው እንዲያጤነው እየጠየቅን በዚህ መንግሥት ላይ ተመሥርቶ ዜናም ይሁን ዘገባ የሚያቀርቡ አካላት ሁለቴ ማሰብ ይገባቸዋል እንላለን።

2ኛ. የግፍ ጭፍጨፋዎች በሙሉ የአብይ አህመድን ወታደሮችን ኮቴ ይከተላሉ:-

የአገዛዙ ወታደሮች በምዕራብ ኦሮሚያ አካባቢዎችን በከፊል ለቀው ከመውጣታቸውና በትግራይ ላይ ጦርነት ከማወጃቸው በፊት አሰቃቂ ጭፍጨፋዎችን ይፈፀሙ ነበር። ለአብነት ኖቨምበር 2020 መጀመሪያ ቀናት በጉሊሶ የፈፀሙትን መጥቀስ ይቻላል። ይሄንንም ግፍ ትግራይ ላይ ጦርነት ለማወጅ እንደ ግብአት ተጠቀሙበት:: በትግራይ በኩል ጦርነቱ በተፋፋመበት ወቅት ግን በወለጋ ምንም አይነት የጅምላ ጭፍጨፋ አልታየም። የኦሮሞ ነፃነት በሺዎች የሚቆጠሩ ወጣቶችን ከመመልመል እና ማሰልጠን በተጓዳኝ በአካባቢው በቀረው የአገዛዙ የጸጥታ ሀይል ላይ ያልተቋረጠ ጥቃት ሲያደርስ ነበር። ሠራዊታችን ለአንዴም ክንዱ ዝሎ የማያውቅ ሲሆን ሲቪሉ ማህረሰብም በአንፃርዊ ሰላም ውስጥ ነበሩ::

ካለፈው አመት ታህሣሥ ወር መጨረሻ ጀምሮ ግን፣ በሰሜን በኩል ያለው ጦርነት በመቀዛቀዙ በወለጋ የአብይ ወታደሮች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ ማደግ የጀመረ ሲሆን የጭካኔ ድርጊቶችና ዘገባዎችም እንዲሁ እየጨመሩ መጡ። በጥር ወር ከነበረው የጊዳሚ እልቂት ጀምሮ የአብይ ወታደሮች በወለጋ በርካታ ዜጎች ላይ ጭካኔ የተሞላበት ድርጊቶችን መፈፀማቸው በተለያዩ ዘገባዎች አመልክተናል።

አገዛዙ በአሁኑ ጊዜ ከሃያ አንድ በላይ የመከላከያ ክፍለ ጦሮችን፣ የልዩ ሀይል እና ሚሊሺያ — ግማሹን የኢትዮጵያ ሰራዊት የሚያህል ማለት ይቻላል — በአብዛኛው በምዕራብ ኦሮሚያ በሚገኙ ሁለት ትናንሽ ዞኖች፡ በቄለም እና በምዕራብ ወለጋ አሰማርቷል። እነዚህም አምስት የኮማንዶ ክፍለ ጦሮችና እና ሁለት የሪፐብሊካን ጥበቃ ክፍለ ጦሮችን ያካትታሉ። አብዛኛዎቹ እነዚህ ሃይሎች ግን ከኃይላችን ጋር በቀጥታ የተዋጉት በተወሰኑና በኛ ሀይል በተወሰዱ የማጥቃት እርምጃዎች ላይ ብቻ ነው። ከዚህ ይልቅ ከዚህ በፊት በዛቱት መሠረት ‘ባህሩን’ ለማድረቅ ሲሉ በየመንገዳቸው ላይ ያገኟቸውን መንደሮችን እያቃጠሉና ህዝቡን እየጨፈጨፉ ነው።

በኦሮሚያ ከወለጋ ዉጭ ባሉ ብዙ ቦታዎች የአማራ እና ሌሎች አናሳ ህዝቦች ይኖራሉ። ለምሳሌ በምዕራብ፣ በሰሜን እና በምስራቅ ሸዋ ዞኖች የኦነሠ አባላት በሚንቀሳቀሱባቸው በርካታ አካባቢዎች አያሌ የአማራ ተወላጆች አሉ። በደቡብ እና በአንዳንድ የምስራቅ ኦሮሚያ ኦነሠ በሚንቀሳቀስባቸውና በተቆጣጠራቸው አካባቢዎችም በተመሳሳይ እንዲሁ ይኖራሉ። ለምንድነው ታዲያ ግፎች የሚፈፀሙት በወለጋ አካባቢ ብቻ እንዲሆን የተመረጠው?

ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የኢትዮጵያን የእርስ በርስ ጦርነት ለመፍታት ሁሉን አቀፍ የሰላም ሂደት እንዲያደራጅ በገዥው አካል ላይ ጫና እያሳደረ መሆኑ ይታወቃል:: የብልጽግና ፓርቲ ግን የኦሮሞን ትግል ለማሳነስና የኦሮሞ ነፃነት ሠራዊትን ለማዳከም የሠራዊቱ ጠንካራ ይዞታ ወደሆነው ወለጋ ወታደራዊ ሀይሉን በከፍተኛ ደረጃ እያጋዘ ሲሆን በዚሁ ተጓዳኝ የሠራዊቱን ሥም ለማጉደፍ፣ ሠራዊቱ ተአማኒ የሠላም ሀይል እንዳልሆነ ለማስመሰል ያመነባቸውን ሁሉንም አይነት የቅጥፈት ተግባራት በዚህ አካባቢ መፈፀሙን ተያይዞታል:: በዚህም ሂደት በኦሮሚያ የሚኖሩ የአማራ ተወላጆች በአራት ኪሎ ቤተ-መንግስት ውስጥ ለሚኖሩ ያለርህራሄ የሚወገዱ የገበጣ ጠጠሮች ሆነውላቸዋል። እንኳን ሰው (ለዚያውም ሴቶችንና ህፃናትን) ቀርቶ እንስሳትን መግደል እና ዛፎችን አለአግባብ መቁረጥ ክልክል በሆነበት የኦሮሞ ባህል ለተወለደና ላደገ ሰው እንዲህ ያለው የሲቪል ሰቆቃ አዙሪት በታሪካችን ታይቶ የማይታወቅና ዘግናኝ ሆኖብናል። በኦሮሚያ የሚኖሩ የአማራ ማህበረሰብ ከኦሮሞ ብሄር ተወላጆች ጋር ለዘመናት በሰላም ኖረዋል ዛሬም ይኖራሉ። ብዙ ሰዎች የማይረዱት ሀቅ ደግሞ በኦሮሚያ ክልል ከሚኖሩ የአማራ ማህበረሰብ አባላት የወጡ የኦሮሞ ነፃነት ሠራዊት አባላትና ብሎም በሰራዊቱ ይዕዝ ሰንሰለት ዉስጥ በአመራር ደረጃ ላይ የሚገኙ መሆናቸዉን ነው።

3ኛ. ለመሆኑ ሸኔ ማነው?

ደጋግመን እንደገለጽነው በአፍሪካ ቀንድ ውስጥ ሸኔ የሚባል የፖለቲካም ሆነ ወታደራዊ ተቋም ወይም ድርጅት የለም። ሸኔ በአብይ መንግስት ለተፈጠሩት ኦሮምኛ ተናጋሪ ገዳይና ዘራፊዎቻቸው ራሳቸው እነአብይ አህመድ የሰጡት ስያሜ ነው። ይህ የኦሮሞ ነፃነት ሠራዊትን በማስመሰል የተደራጀውና በሰንቀሌ ፖሊስ ማሰልጠኛ ለብዙ ዙሮች የሠለጠነው ፓራ ሚሊታሪ በኦሮሚያ ብቻ ሳይሆን በቤኒሻንጉል እና አማራ ክልሎች ተሠማርተው አፀያፊ ድርጊቶችን እንዲፈጽሙ በአብይ አህመድ እና በተባባሪዎቹ የሚታዘዙና የሚሠማሩ ሀይሎች ናቸው።

4ኛ. በሀገር ውስጥ አካላት የሚደረግ ምርመራ ተቀባይነት የለዉም።

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ራሱን የቻለ የሰብአዊ መብት ተሟጋች አካል ተደርጎ የሚመሰል፣ ነገር ግን በህግም ሆነ በተግባር በመንግስት በጀት የሚንቀሳቀስ የመንግሥት አካል ነው። ተቋሙ እና ኮሚሽነሮቹ በተለይ ለኦሮሚያ፣ ለኦሮሞ ህዝብ እና ለኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት፣ እንደ ተቋምም ሆነ እንደግለሰብ ተአማኒም ገለልተኛም አይደሉም። በቅርብ ጊዜ ብቻ የተከሰቱ ሁለት ክስተቶችን እንመልከት፡-

ሀ. ባለፈው አመት፣ ታህሣሥ ወር ላይ በወሎ ኦሮሞዎች ላይ የተፈፀመውን ጭፍጨፋ የሚያሳይ ቪዲዮ ከጥቂት ሳምንታት በፊት ብቅ ሲል፣ ኢሰመኮ የወንጀለኞቹን ማንነት ሳይጠቅስ ወዲያውኑ በጉዳዩ ላይ ጥልቅ ምርመራ እንደሚያደርግ ገልጿል። በተቃራኒው፣ በጊምቢ የቶሌ እልቂት ከሁለት ሳምንት በፊት ሲነገር፣ ምንም አይነት ምርመራ ሳይደረግበት፣ ዜናው በተሰማ ቀን፣ በሪፖርቱ ኦነግ-ኦነሠን ወቅሷል። ተጎጂዎችንም የአንድ ብሔር አባላት ብቻ አስመስሎ አቅርቧል::

ለ. በቄሌም ወለጋ በሃዋ ገላን ወረዳ የደረሰውን የጅምላ ጭፍጨፋ መዘገቡን ተከትሎ፣ ዜናው በተሰማ ዕለት፣ ኢሰመኮ በድጋሚ ያለምንም ማጣራት ወንጀለኛውን ኦነግ ነው ብሏል:: የመንግስት የጸጥታ ሃይሎች ወደ አካባቢው በፍጥነት እንዲሰማሩም ምክረ ሀሳብ የሰጠ ሲሆን ይህም አገዛዙን ከተጠያቂነት ነጻ ለማድረግ የታለመ ነው።

ስለዚህም በሀገሪቱ ውስጥ የተፈጸሙትን ጭፍጨፋዎች ሁሉ በገለልተኛ ዓለም አቀፍ የምርመራ አካል እንዲጣራ፣ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ በገዥው አካል ላይ ጫና እንዲያደርግ ደግመን እንጠይቃለን። በዚህ ረገድ በሰሜኑ የኢትዮጵያ ክፍል የተፈፀመውን የዘር

ፍጅት ለመመርመር የተቋቋመው አለም አቀፍ ኮሚቴ የስራ ጊዜውንና ቦታውን በማስፋት፣ በመላው ሀገሪቱ እንዲሰማራ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብአዊ መብቶች ኮሚሽንን እንጠይቃለን።

5ኛ. ህዝባችን ምን ማድረግ አለበት?

አገዛዙ በተበላሸ የፖለቲካ ስሌት ሰለባ እያደረጋቸው ያሉትን የአማራ ብሔር ተወላጆች የኦሮሞ ህዝብ በተቻለው መጠን እንዲከላከል ጥሪያችንን እናቀርባለን። የኦሮሞ ህዝብ እራሱም የስርዐቱ ሰለባ እንደሆነ ብንረዳም፣ በመረጃና በሌላም በተቻለ መንገድ ሁሉ ከጎናቸው እንዲቆም እንጠይቃለን:: በአገዛዙ ሰራዊት ውስጥ ያሉ ወንድም እና እህቶቻችን ይሄንን ህፃናት ጨፍጫፊ የፋሺስቶች ቡድን በመተው በንፁሓንና ነፃነት ናፋቂ ወንድሞቻችሁ ወደተገነባው የኦሮሞ ነፃነት ሰራዊት እንድትመጡና ቢያንስ ከዚህ ፀረ-ህዝብ የወንጀል ቡድን ራሳችሁን እንድታድኑ ጥሪያችንን እናቀርባለን:: ውድ በክልላችን የምትኖሩ ወንድም የአማራ ማህረሰብ አባላት፣ በግራም ይሁን በቀኝ በደማችሁ የፖለቲካ ቁማር የሚጫወቱ ሀይሎችን ነቅታችሁ በመከታተል ከኦሮሞ ወንድሞቻችሁ ጋር እጅ ለጅ በመያያዝ ለሰው ልጆች ነፃነት ዋጋ ከሚሰጠው የኦሮሞ ነፃነት ሠራዊት ጎን እንድትሰለፉ ጥሪያችንን እናቀርባለን:: እኛ ካልታጠቀና ራሱን እንኳ መከላከል ከማይችል ለፍቶ አዳሪ ገበሬ ጋር ጠብ የለንም::

6ኛ. ከአለም አቀፉ ማህረሰብ ምን ይጠበቃል?

የአብይ መንግስት ሁሉንም ያሳተፈ የፖለቲካ ሂደትን ከመተግበር ይልቅ ‘በሰላም ድርድር’ ስም በሰሜናዊው የሀገሪቱ ክፍል የተፈጠረውን አንፃራዊ መረጋጋት ተጠቅሞ በኦሮሚያ ውስጥ ያለውን የተቃውሞ ድምፅ ለማጥፋት ሌት ተቀን እየሰራ ነው። ስለዚህ አለም አቀፉ ማህበረሰብ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ያለዉን ግንኙነት ለማሻሻል ከሚያስቀምጣቸው ቅድመ ሁኔታዎች መካከል፣የኦሮሚያ ሁኔታ መሻሻል እንደ አንዱ አድርጎ እንዲወስድ እናሳስባለን:: በዚህ በሀገሪቱ በቆዳ ስፋቱም ሆነ፣ በህዝብ ብዛቱ እንዲሁም በተፈጥሮ ሀብቱ ትልቁ በሆነው ኦሮሚያ ሰላምና መረጋጋት ሳይፈጠር ቀጠናውን ማረጋጋት ከቶውን አይታሰብም:: በተለይም ይህ መንግሥት ለፖለቲካ ቁማሩ ሲል የሚያፈሰውን የንፁሀን ደም በአስቸኳይ ካላቆመ ይህ ሀገርና ቀጠናው ከማይወጡበት አዘቅት ውስጥ እንደሚገቡ በአግባቡ እንዲረዱት ደጋግመን እናሳስባለን:: ማንኛውም አለም አቀፍ ተዋናይ ለዚህ ፋሺስታዊ መንግሥት የሚሰጠውን ፖለቲካዊ፣ ዲፕሎማሲያዊ፣ ወታደራዊና ኢኮኖሚያዊ እርዳታ ከህዝቦች ሰብአዊ መብት መከበር ጋር ካላስተሳሰረ በሚፈፀሙት ወንጀሎችም ነገ ከታሪክ ተጠያቂነት መዳን አይቻልም።

ለአፍሪካ ቀንድ መረጋጋት የኦሮሚያ ሰላም ወሳኝ ነው!

የኦነግ-ኦነሠ ከፍተኛው ዕዝ

ጁላይ 5፣ 2022

Leave a Reply

Discover more from Qeerroo Bilisummaa Oromoo

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading